መጋቢት ፬(አራት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የተለያዩ ክልሎችን የሚሸፍነው ሪፖርት፣ በዜጎች ላይ የተፈጸሙ ዝርዝር ጥቃቶችን አቅርቧል። በትግራይ ክልል በአጽቢወንበርታ ምርጫ ክልል ለሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት የመድረክ ዕጩ ተወዳዳሪ የሆኑት አቶ ወ/ገብርኤል ኃይሉ የዕጩነት መታወቂያ እንደያዙ ተይዘው ከታሰሩ በኋላ የአስር ወራት የእስራት ቅጣት ተፈርዶባቸዋል፡፡
“በቆላ ተንቤን ወረዳ በወርቅ አምባ ምርጫ ክልል የክልል ም/ቤት ዕጩ ተወዳዳሪ የሆኑት አቶ ብርሃን ንጉስ ተክለእግዚም በተመሳሳይ ሁኔታ የዕጩነት መታወቂያቸውን እንደያዙ ተይዘው ከታሰሩ በኋላ የሶስት ዓመት የእስራት ቅጣት ተፈርዶባቸዋል፡፡”
” ወ/ሮ ቤራይ ገብሩ የሚባሉ በሁመራ ምርጫ ክልል የክልል ም/ቤት ዕጩ ተወዳዳሪ ደግሞ ከታሰሩ በኋላ ተፈትተዋል፡፡ የአቶ ወ/ገብርኤል ኃይሉ የእርሻ መሬትም ተነጥቆ የሕወሐት አባላት ለሆኑ ወጣቶች ተሰጥቷል፡፡ “
በሁመራ ምርጫ ክልል የአረና/መድረክ አባል የሆኑት ቄስ ህሉፍ ካህሳይና በቆላ ተንቤን የአረና/መድረክ አባል የሆኑት አቶ ዜናዊ አስመላሽም በፖሊስ፣ በኢህአዴግ ካድሬዎችና በአከባቢ ሚሊሺያዎች ተደብድበው ለከፍተኛ ጉዳት ተዳርገዋል፡፡