ሳሙኤል አወቀ እስር፣ ድብደባ፣ ዛቻ እየተደረገበት ወደኋላ ሳይል ሲታገል የቆየ ወጣት ነው፡፡ በርካታ ምሁራን ቤታቸው ቁጭ ባሉበት ይህ ወጣት በድፍረት የምስኪኑን አርሶ አደር ስቃይ በየቀኑ ለሚዲያ ሲያጋልጥ ቆይቷል፡፡
ለዚህ ሁሉ ግን በቀል ተፈፅሞበታል፡፡ ለነገዋ ኢትዮጵያ፣ ለነፃነት ያለመው ወጣት በትናንትናው ዕለት ተገድሎ ተገኝቷል፡፡ ይህ ወጣት ከቀናት በፊት ይህን ፅፎ ነበር፡፡
እናስርሃለን፣ እንገድልሃለን!
(የገዥዎቻችን የሥራና የመግባቢያ ቋንቋ)
ሳሙኤል አወቀ
“ሀገሬ፣ ታሪክ፣ ሐይማኖት፣ ባሕልና ሸማግሌዎች አሏት፡፡ ነገር ግን ምነው ትንፍሽ የሚል ጠፋ? በየቀበሌው ጠያቂ የሌለው ጥቃቅን ንጉስ ነግሶብናል:: በደል እና ግፍ ራሳቸው እየፈፀሙ ለራሳቸው እንድንሰግድ የሚያደርግሥርዓት ተበጅቷል:: የቀበሌ ካድሬ የፍርድ ቤት ውሳኔ እንኳን አይገዛውም:: አላምንበትም አልተማከርሁበትም ይላል:: ወደየት ይደረሳል? ለማንስ ይነገራል? ከተመደበለት የቀበሌ ኮሚኒቲ ፖሊስ ጋር አብሮ ያስራል፡፡ ይገርፋል፡፡ ይደበድባል፡፡ ሲፈልግ የሀሠት ምሰክር አደራጅቶ እሰር ቤት ያሰወረውራል፡፡ የህዝብ ሮሮ ለነሱ ሙዚቃ ሆኗል፡፡ ሀይ ባይ፣ ገላጋይ፣ ገሳጭ አሥታራቂ ሽማግሌዎች እና የኃይማኖት መሪዎች በዓለማዊ ሕይወት ሕዝባቸውን ረስተዋል፡፡